← SongOfSongs (8/8) |
1. | አንተ የእናቴን ጡት እንደ ጠባ እንደ ወንድሜ ምነው በሆንህ! በሜዳ ባገኘሁህ ጊዜ በሳምሁህ፥ ማንም ባልናቀኝም ነበር። |
2. | መርቼ ወደ እናቴ ቤት ባገባሁህ፥ በዚያም አንተ ባስተማርከኝ፤ እኔም ከመልካሙ ወይን ጠጅ ከሮማኔም ውኃ ባጠጣሁህ ነበር። |
3. | ግራው ከራሴ በታች በሆነች ቀኙም ባቀፈችኝ ነበር። |
4. | እናንተ የኢየሩሳሌም ቈነጃጅት ሆይ፥ እርሱ እስኪፈልግ ድረስ ፍቅርን እንዳታስነሡት እንዳታነሣሡትም አምላችኋለሁ። |
5. | በውድዋ ላይ ተደግፋ ከምድረ በዳ የምትወጣ ይህች ማን ናት? ከእንኮይ በታች አስነሣሁህ፤ በዚያ እናትህ ወለደችህ፥ በዚያም ወላጅ እናትህ አማጠችህ። |
6. | እንደ ማኅተም በልብህ፥ እንደ ማኅተም በክንድህ አኑረኝ፤ ፍቅር እንደ ሞት የበረታች ናትና፥ ቅንዓትም እንደ ሲኦል የጨከነች ናትና። ፍንጣሪዋ እንደ እሳት ፍንጣሪ፥ እንደ እግዚአብሔር ነበልባል ነው። |
7. | ብዙ ውኃ ፍቅርን ያጠፋት ዘንድ አይችልም፥ ፈሳሾችም አያሰጥሙአትም፤ ሰው የቤቱን ሀብት ሁሉ ስለ ፍቅር ቢሰጥ ፈጽሞ ይንቁታል። |
8. | እኛ ጡት የሌላት ታናሽ እኅት አለችን፤ ስለ እርስዋ በሚናገሩባት ቀን ለእኅታችን ምን እናድርግላት? |
9. | እርስዋ ቅጥር ብትሆን የብር ግንብ በላይዋ እንሠራለን፤ ደጅም ብትሆን በዝግባ ሳንቃ እንከብባታለን። |
10. | እኔ ቅጥር ነኝ ጡቶቼም እንደ ግንብ ናቸው፤ በዚያን ጊዜ በፊቱ ሰላምን እንደምታገኝ ሆንሁ። |
11. | ለሰሎሞን በብኤላሞን የወይን ቦታ ነበረው፤ የወይኑን ቦታ ለጠባቂዎች አከራየው፤ ሰው ሁሉ ለፍሬው ሺህ ብር ያመጣለት ነበር። |
12. | ለእኔ ያለኝ የወይን ቦታ በፊቴ ነው፤ ሰሎሞን ሆይ፥ ሺሁ ለአንተ፥ ሁለት መቶውም ፍሬውን ለሚጠብቁ ይሆናል። |
13. | በገነቱ የምትቀመጪ ሆይ፥ ባልንጀሮች የአንቺን ቃል ያደምጣሉ፤ ቃልሽን አሰሚኝ። |
14. | ውዴ ሆይ፥ ፍጠን፤ በቅመም ተራራ ላይ ሚዳቋን ወይም የዋላን እምቦሳ ምሰል። |
← SongOfSongs (8/8) |