Lamentations (1/5) → |
1. | አሌፍ። ሕዝብ ሞልቶባት የነበረች ከተማ ብቻዋን እንዴት ተቀመጠች! በአሕዛብ መካከል ታላቅ የነበረች እንደ መበለት ሆናለች፤ በአውራጆች መካከል ልዕልት የነበረች ተገዢ ሆናለች። |
2. | ቤት። በሌሊት እጅግ ታላቅሳለች፥ እንባዋም በጕንጭዋ ላይ አለ፤ ከውሽሞችዋ ሁሉ የሚያጽናናት የለም፤ ወዳጆችዋ ሁሉ ወነጀሉአት ጠላቶችም ሆኑአት። |
3. | ጋሜል። ይሁዳ ስለ መጨነቅና ስለ ባርነት ብዛት ተማረከች፤ በአሕዛብ መካከል ተቀመጠች ዕረፍትም አላገኘችም፤ የሚያስጨንቁአት ሁሉ ተጨንቃ አገኙአት። |
4. | ዳሌጥ። ወደ ዓመት በዓልም የሚመጣ የለምና የጽዮን መንገዶች አለቀሱ፤ በሮችዋ ሁሉ ፈርሰዋል ካህናቶችዋም እየጮኹ ያለቅሳሉ፤ ደናግሎችዋም ተጨነቁ እርስዋም በምሬት አለች። |
5. | ሄ። ስለ ኃጢአትዋ ብዛት እግዚአብሔር አስጨንቆአታልና አስጨናቂዎችዋ ራስ ሆኑ ጠላቶችዋም ተከናወነላቸው፤ ሕፃናቶችዋ በአስጨናቂዎች ፊት ተማርከዋል። |
6. | ዋው። ከጽዮን ሴት ልጅ ውበትዋ ሁሉ ወጥቶአል፤ አለቆችዋ ማሰማርያ እንደማያገኙ ዋላዎች ሆኑ፤ ከሚያባርሩአቸው ፊት ተዳክመው ሄዱ። |
7. | ዛይ። ኢየሩሳሌም በጭንቀትዋና በመከራዋ ወራት ከጥንት ጀምሮ የነበረላትን የከበረን ነገር ሁሉ አሰበች፤ ሕዝብዋ በአስጨናቂዎች እጅ በወደቀ ጊዜ የሚረዳትም በሌላት ጊዜ፥ አስጨናቂዎች አዩአት በመፍረስዋም ሳቁ። |
8. | ሔት። ኢየሩሳሌም እጅግ ኃጢአት ሠርታለች፤ ስለዚህ ረክሳለች፤ ያከብሩአት የነበሩ ሁሉ ኀፍረተ ሥጋዋን አይተዋታልና አቃለሉአት፤ እርስዋም እየጮኸች ታለቅሳለች ወደ ኋላም ዘወር አለች። |
9. | ጤት። አደፍዋ በልብስዋ ዘርፍ ነበረ፤ ፍጻሜዋን አላሰበችም፤ ስለዚህ በድንቅ ተዋርዳለች፥ የሚያጽናናትም የለም፤ አቤቱ፥ ጠላት ከፍ ከፍ ብሎአልና መከራዬን ተመልከት። |
10. | ዮድ። አስጨናቂው በከበረ ነገርዋ ሁሉ ላይ እጁን ዘረጋ፤ ወደ ጉባኤህ እንዳይገቡ ያዘዝሃቸው አሕዛብ ወደ መቅደስዋ ሲገቡ አይታለችና። |
11. | ካፍ። ሕዝብዋ ሁሉ እየጮኹ ያለቅሳሉ እንጀራም ይፈልጋሉ፤ ሰውነታቸውን ለማበርታት የከበረ ሀብታቸውን ስለ መብል ሰጥተዋል፤ አቤቱ፥ ተጐሳቍያለሁና እይ፥ ተመልከትም። |
12. | ላሜድ። እናንተ መንገድ አላፊዎች ሁሉ፥ በእናንተ ዘንድ ምንም የለምን? እግዚአብሔር በጽኑ ቍጣው ቀን እኔን እንዳስጨነቀበት በእኔ ላይ እንደ ተደረገው እንደ እኔ መከራ የሚመስል መከራ እንዳለ ተመልከቱ፥ እዩ። |
13. | ሜም። ከላይ እሳትን ወደ አጥንቴ ሰደደ በረታችበትም፤ ለእግሬ ወጥመድ ዘረጋ ወደ ኋላም መለሰኝ፥ አጠፋኝም ቀኑንም ሁሉ አደከመኝ። |
14. | ኖን። የኃጢአቶቼ ቀንበር በእጁ ተይዛለች፤ ታስረው በአንገቴ ላይ ወጥተዋል፤ ጕልበቴን አደከመ። ጌታ በፊታቸው እቆም ዘንድ በማልችላቸው እጅ አሳልፎ ሰጠኝ። |
15. | ሳምኬት። ጌታ ኃያላኖቼን ሁሉ ከውስጤ አስወገዳቸው፤ ጕልማሶቼን ያደቅቅ ዘንድ ጉባኤን ጠራብኝ፤ ጌታ ድንግሊቱን የይሁዳን ልጅ በመጥመቂያ እንደሚረገጥ አድርጎ ረገጣት። |
16. | ዔ። የሚያጽናናኝ ነፍሴንም የሚያበረታት ከእኔ ርቆአልና ስለዚህ አለቅሳለሁ፤ ዓይኔ፥ ዓይኔ ውኃ ያፈስሳል። ጠላት በርትቶአልና ልጆቼ ጠፍተዋል። |
17. | ፌ። ጽዮን እጅዋን ዘረጋች፤ የሚያጽናናት የለም፤ እግዚአብሔር በያዕቆብ ዙሪያ ያሉትን እንዲያስጨንቁት አዘዘ፤ ኢየሩሳሌም በመካከላቸው እንደ ርኩስ ነገር ሆናለች። |
18. | ጻዴ። በአፉ ነገር ላይ ዓመፅ አድርጌአለሁና እግዚአብሔር ጻድቅ ነው። እናንተ አሕዛብ ሁሉ፥ እባካችሁ፥ ስሙ መከራዬንም ተመልከቱ፤ ደናግሎቼና ጐበዛዝቴ ተማርከው ሄዱ። |
19. | ቆፍ። ውሽሞቼን ጠራሁ እነርሱም አታለሉኝ፤ ካህናቶቼና ሽማግሌዎቼ ሰውነታቸውን ያበረቱ ዘንድ መብል ሲፈልጉ በከተማ ውስጥ ሞቱ። |
20. | ሬስ። አቤቱ፥ ተጨንቄአለሁና፥ አንጀቴም ታውኮብኛልና ተመልከት፤ ዓመፃን ፈጽሞ አድርጌአለሁና ልቤ በውስጤ ተገላበጠብኝ፤ በሜዳ ሰይፍ ልጆቼን አጠፋ በቤትም ሞት አለ። |
21. | ሳን። እኔ እየጮኽሁ እንደማለቅስ ሰምተዋል፤ የሚያጽናናኝ የለም፤ ጠላቶቼ ሁሉ ስለ መከራዬ ሰምተዋል፤ አንተ አድርገኸዋልና ደስ አላቸው፤ ስለ እርሱ የተናገርኸውን ቀን ታመጣለህ እነርሱም እንደ እኔ ይሆናሉ። |
22. | ታው። ልቅሶዬ እጅግ ነውና፥ ልቤም ደክሞአልና ክፋታቸው ሁሉ ወደ ፊትህ ይድረስ፥ ስለ ኃጢአቴ ሁሉ እንዳደረግህብኝ አድርግባቸው። |
Lamentations (1/5) → |