Judges (12/21)  

1. የኤፍሬም ሰዎች ተሰበሰቡ፥ ወደ ጻፎንም ተሻግረው ዮፍታሔን። ከአሞን ልጆች ጋር ለመዋጋት ስታልፍ ከአንተ ጋር እንድንሄድ ስለ ምን አልጠራኸንም? ቤትህን በአንተ ላይ በእሳት እናቃጥለዋለን አሉት።
2. ዮፍታሔም። ከአሞን ልጆች ጋር ለእኔና ለሕዝቤ ጽኑ ጠብ ነበረን፤ በጠራኋችሁም ጊዜ ከእጃቸው አላዳናችሁኝም።
3. እንዳላዳናችሁኝም ባየሁ ጊዜ ነፍሴን በእጄ አድርጌ በአሞን ልጆች ላይ አለፍሁ፥ እግዚአብሔርም በእጄ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ለምንስ ዛሬ ልትወጉኝ ወደ እኔ መጣችሁ? አላቸው።
4. ዮፍታሔም የገለዓድን ሰዎች ሁሉ ሰበሰበ፥ ከኤፍሬምም ጋር ተዋጋ፤ ኤፍሬምም። ገለዓዳውያን ሆይ፥ እናንተ በኤፍሬምና በምናሴ መካከል የተቀመጣችሁት ከኤፍሬም ሸሽታችሁ ነው ስላሉ የገለዓድ ሰዎች ኤፍሬምን መቱ።
5. ገለዓዳውያንም ኤፍሬም የሚያልፍበትን የዮርዳኖስን መሻገሪያ ያዙባቸው፤ የሸሸም የኤፍሬም ሰው። ልለፍ ባለ ጊዜ፥ የገለዓድ ሰዎች። አንተ ኤፍሬማዊ ነህን? አሉት፤ እርሱም። አይደለሁም ቢል፥
6. እነርሱ። አሁን ሺቦሌት በል አሉት፤ እርሱም አጥርቶ መናገር አልቻለምና። ሲቦሌት አለ፤ ይዘውም በዮርዳኖስ መሻገሪያ አረዱት፤ በዚያም ጊዜ ከኤፍሬም አርባ ሁለት ሺህ ሰዎች ወደቁ።
7. ዮፍታሔም በእስራኤል ላይ ስድስት ዓመት ፈረደ። ገለዓዳዊውም ዮፍታሔ ሞተ፥ ከገለዓድም ከተሞች በአንዲቱ ተቀበረ።
8. ከእርሱም በኋላ የቤተ ልሔሙ ኢብጻን በእስራኤል ላይ ፈራጅ ሆነ።
9. ሠላሳም ወንዶች ልጆችና ሠላሳ ሴቶች ልጆች ነበሩት፤ ሠላሳ ሴቶች ልጆቹንም ወደ ውጭ አገር ዳረ፤ ለወንዶች ልጆቹም ከውጭ አገር ሴቶች ልጆችን አመጣ። በእስራኤልም ላይ ሰባት ዓመት ፈረደ።
10. ኢብጻንም ሞተ፥ በቤተ ልሔምም ተቀበረ።
11. ከእርሱም በኋላ ዛብሎናዊው ኤሎም በእስራኤል ላይ ፈራጅ ሆነ፤ እርሱም በእስራኤል ላይ አሥር ዓመት ፈረደ።
12. ዛብሎናዊውም ኤሎም ሞተ፥ በዛብሎንም ምድር ባለችው በኤሎም ተቀበረ።
13. ከእርሱም በኋላ የጲርዓቶናዊው የሂሌል ልጅ ዓብዶን በእስራኤል ላይ ፈራጅ ሆነ።
14. አርባም ልጆች ሠላሳም የልጅ ልጆች ነበሩት፤ በሰባም አህያ ግልገሎች ላይ ይቀመጡ ነበር። በእስራኤልም ላይ ስምንት ዓመት ፈረደ።
15. የጲርዓቶናዊውም የሂሌል ልጅ ዓብዶን ሞተ፥ በተራራማውም በአማሌቃውያን ምድር በኤፍሬም ባለችው በጲርዓቶን ተቀበረ። a

  Judges (12/21)