Job (41/42)  

1. እነሆ፥ ተስፋው ከንቱ ነው፤ ያየው ሁሉ ስንኳ በፊቱ ይዋረዳል።
2. ያንቀሳቅሰውም ዘንድ የሚደፍር የለም፤ እንግዲህ በፊቴ መቆም የሚችል ማን ነው?
3. እመልስለትስ ዘንድ መጀመሪያ የሰጠኝ ማን ነው? ከሰማይ ሁሉ በታች ያለው ገንዘቤ ነው።
4. ስለ አካላቱና ስለ ብርቱ ኃይሉ፥ ስለ መልካም ሰውነቱ ዝም አልልም።
5. የውጪ ልብሱን ማን ይገፋል? በጥንድ መንጋጋውስ ውስጥ ማን ይገባል?
6. የፊቱንስ ደጆች የሚከፍት ማን ነው? በጥርሶቹ ዙሪያ ግርማ አለ።
7. ቅርፊቶቹ ጠንካራ ስለ ሆኑ እርሱ ትዕቢተኛ ነው፤ በጠባብ ማተሚያ እንደ ታተሙ ናቸው።
8. እርስ በርሳቸው የተቀራረቡ ናቸውና ነፋስ በመካከላቸው መግባት አይችልም።
9. እርስ በርሳቸው የተገጣጠሙ ናቸው፤ እስከማይለያዩም ድረስ ተያይዘዋል።
10. እንጥሽታው ብልጭታ ያወጣል፥ ዓይኖቹም እንደ ወገግታ ናቸው።
11. ከአፉ ፋናዎች ይወጣሉ፥ የእሳትም ፍንጣሪ ይረጫል።
12. እንደ ፈላ ድስትና እንደሚቃጠል ሸምበቆ ከአንፍንጫው ጢስ ይወጣል።
13. እስትንፋሱ ከሰልን ታቃጥላለች፥ ነበልባልም ከአፉ ይወጣል።
14. በአንገቱ ኃይል ታድራለች፤ ግርማ በፊቱ ይዘፍናል።
15. የሥጋውም ቅርፊት የተጣበቀ ነው፤ እስከማይንቀሳቀሱም ድረስ በእርሱ ላይ ጸንተዋል።
16. ልቡ እንደ ድንጋይ የደነደነ ነው፤ እንደ ወፍጮ ድንጋይ የጸና ነው።
17. በተነሣ ጊዜ ኃያላን ይፈራሉ፤ ከድንጋጤም የተነሣ ያብዳሉ።
18. ሰይፍና ጦር፥ ፍላጻና መውጊያም ቢያገኙት አያሸንፉትም።
19. ብረትን እንደ ገለባ፥ ናስንም እንደ ነቀዘ እንጨት ይቈጥራቸዋል።
20. ፍላጻ ሊያባርረው አይችልም፤ የወንጭፍም ድንጋዮች እንደ ገለባ ይሆኑለታል።
21. በሎታውን እንደ ገለባ ይቈጥረዋል፤ ሰላጢኑም ሲሰበቅ ይስቃል።
22. ታቹ እንደ ስለታም ገል ነው፤ እንደ መዳመጫም በጭቃ ላይ ያልፋል።
23. ቀላዩን እንደ ድስት ያፈላዋል፤ ባሕሩንም እንደ ሽቱ ምንቸት ያደርገዋል።
24. በስተ ኋላው ብሩህ መንገድን ያበራል፤ ቀላዩም ሽበት ይመስላል።
25. ያለ ፍርሃት የተፈጠረ፥ እንደ እርሱ ያለ በምድር ላይ የለም።
26. ከፍ ያለውን ሁሉ ይመለከታል፤ በትዕቢተኞችም ሁሉ ላይ ንጉሥ ነው።

  Job (41/42)