| ← Job (27/42) → |
| 1. | ኢዮብም ምሳሌውን ይመስል ዘንድ ደገመ፥ እንዲህም አለ። |
| 2. | ፍርዴን ያስወገደ ሕያው እግዚአብሔርን! ነፍሴንም መራራ ያደረገ ሁሉን የሚችል ሕያው አምላክን! |
| 3. | እስትንፋሴ በእኔ ውስጥ፥ የእግዚአብሔርም መንፈስ በአፍንጫዬ ውስጥ ገና ሳለ፥ |
| 4. | ከንፈሬ ኃጢአትን አትናገርም፥ አንደበቴም ሽንገላን አያወጣም። |
| 5. | እናንተን ማጽደቅ ከእኔ ዘንድ ይራቅ፤ እስክሞት ድረስ ፍጹምነቴን ከእኔ አላርቅም። |
| 6. | ጽድቄን እይዛለሁ እርሱንም አልተውም፤ ከቀኖቼም ሁሉ ስለ አንዱ ልቤ አይዘልፈኝም። |
| 7. | ጠላቴ እንደ በደለኛ፥ በእኔ ላይም የሚነሣ እንደ ኃጢአተኛ ይሁን። |
| 8. | እግዚአብሔር ባጠፋውና ነፍሱን በለየ ጊዜ፥ የዝንጉ ሰው ተስፋው ምንድር ነው? |
| 9. | በውኑ መከራ በመጣበት ጊዜ፥ እግዚአብሔር ጩኸቱን ይሰማልን? |
| 10. | ሁሉንስ በሚችል አምላክ ደስ ይለዋልን? እግዚአብሔርንስ ሁልጊዜ ይጠራልን? |
| 11. | እኔ ስለ እግዚአብሔር እጅ አስተምራችኋለሁ፤ ሁሉን በሚችል አምላክ ዘንድ ያለውን አልሸሽግም። |
| 12. | እነሆ፥ ሁላችሁ አይታችኋል፤ ስለ ምን ከንቱ ሆናችሁ? |
| 13. | ይህች ከእግዚአብሔር ዘንድ የበደለኛ እድል ፈንታ፥ ግፈኛም ሁሉን ከሚችል አምላክ ዘንድ የሚቀበላት ርስት ናት፤ |
| 14. | ልጆቹ ቢበዙ ለሰይፍ ይሆናሉ፤ ዘሩም እንጀራን አይጠግብም። |
| 15. | ለእርሱም የቀሩት በቸነፈር ይቀበራሉ፤ መበለቶቻቸውም አያለቅሱም። |
| 16. | እርሱ ብርን እንደ አፈር ቢከምር፥ ልብስንም እንደ ጭቃ ቢያዘጋጅ፥ |
| 17. | እርሱ ያዘጋጀው ይሆናል፥ ነገር ግን ጻድቅ ይለብሰዋል፤ ብሩንም ንጹሐን ይከፋፈሉታል። |
| 18. | የሚሠራው ቤት እንደ ሸረሪት ድር ይሠራል፥ ጠባቂም እንደሚሠራው ጎጆ ነው። |
| 19. | ባለጠጋ ሆኖ ይተኛል፥ ዳግመኛም አይተኛም፤ ዓይኑን ይከፍታል፥ እርሱም የለም። |
| 20. | ድንጋጤ እንደ ጐርፍ ታገኘዋለች፤ በሌሊትም ዐውሎ ነፋስ ትነጥቀዋለች። |
| 21. | የምሥራቅ ነፋስ ያነሣዋል፥ እርሱም ይሄዳል፤ ከቦታውም ይጠርገዋል። |
| 22. | እርሱ ይጥልበታል፥ አይራራለትም፤ ከእጁ ፈጥኖ መሸሽ ይወድዳል። |
| 23. | ሰው በእጁ ያጨበጭብበታል፤ ከስፍራውም በፉጨት ያስወጡታል። |
| ← Job (27/42) → |