Job (24/42)  

1. ሁሉን ከሚችል አምላክ ዘንድ ዘመናት አልተሰወረምና እርሱን የሚያውቁ ለምን ወራቱን አያዩም?
2. የድንበሩን ምልክት የሚያፈርሱ አሉ፤ መንጋዎቹን በዝብዘው ያሰማራሉ።
3. የድሀ አድጎቹን አህያ ይነዳሉ፤ የመበለቲቱን በሬ ስለ መያዣ ይወስዳሉ።
4. ድሆቹን ከመንገዱ ያወጣሉ፤ የምድርም ችግረኞች ሁሉ ይሸሸጋሉ።
5. እነሆ፥ በምድረ በዳ እንዳሉ እንደ ሜዳ አህዮች፥ መብልን ፈልገው ወደ ሥራቸው ይወጣሉ፤ ምድረ በዳውም ለልጆቻቸው መብልን ይሰጣቸዋል።
6. እነዚያ በእርሻ ውስጥ እህላቸውን ያጭዳሉ፤ የበደለኛውንም ወይን ይቃርማሉ።
7. ራቁታቸውን ያለ ልብስ ያድራሉ፥ በብርድ ጊዜ መጐናጸፊያ የላቸውም።
8. ከተራሮች በሚወርድ ዝናብ ይረጥባሉ፤ መጠጊያም አጥተው ቋጥኙን ያቅፋሉ።
9. ድሀ አደጉን ልጅ ከጡቱ የሚነጥሉ አሉ ከችግረኛውም መያዣ ይወስዳሉ።
10. ያለ ልብስ ራቁታቸውን ይሄዳሉ፤ ተርበውም ነዶዎችን ይሸከማሉ፤
11. በእነዚህ ሰዎች አጥር ውስጥ ዘይት ያደርጋሉ፤ ወይንም ይጠምቃሉ፥ ነገር ግን ይጠማሉ።
12. ከከተማውና ከገዛ ቤቶቻቸው ይባረራሉ፤ የልጆችም ነፍስ ለእርዳታ ትጮኻለች፤ እግዚአብሔር ግን ስንፍናቸውን አይመለከትም።
13. እነዚህ በብርሃን ላይ የሚያምፁ ናቸው፤ መንገዱን አያውቁም፥ በጎዳናውም አይጸኑም።
14. ነፍሰ ገዳዩም ሳይነጋ ማልዶ ይነሣል፤ ችግረኞችንና ድሆችን ይገድላል፤ በሌሊትም እንደ ሌባ ነው።
15. የአመንዝራም ዓይን ድግዝግዝታን ይጠብቃል። የማንም ዓይን አያየኝም ይላል፥ ፊቱንም ይሸፍናል።
16. ቤቶቹን በጨለማ ይነድላሉ፤ በቀን ይሸሸጋሉ፤ ብርሃንም አያውቁም።
17. የጥዋት ብርሃን ለእነርሱ ሁሉ እንደ ሞት ጥላ ነው፤ የሞትን ጥላ ድንጋጤ ያውቃሉና።
18. እነርሱ በውኃ ፊት ላይ በርረው ያልፋሉ፤ እድል ፈንታቸውም በምድር ላይ የተረገመች ናት፤ ወደ ወይኑ ቦታ መንገድ አይዞሩም።
19. ድርቅና ሙቀት የአመዳዩን ውኃ ያጠፋሉ፤ እንዲሁ ሲኦል በደለኞችን ታጠፋለች።
20. ማኅፀን ትረሳዋለች፤ ትልም በደስታ ይጠባዋል፤ ዳግመኛም አይታሰብም፤ ክፋትም እንደ ዛፍ ይሰበራል።
21. የማትወልደውን መካኒቱን ይበድላታል፤ ለመበለቲቱም በጎነት አያደርግም።
22. ነገር ግን በኃይሉ ኃያላንን ይስባል፤ እርሱም በተነሣ ጊዜ ሰው በሕይወቱ አይታመንም።
23. እግዚአብሔር በደኅና አኑሮአቸዋል፥ በዚያም ይታመናሉ፤ ዓይኖቹ ግን በመንገዳቸው ላይ ናቸው።
24. ጥቂት ጊዜ ከፍ ከፍ ይላሉ፤ ይሄዳሉ፥ ይጠወልጋሉም፤ እንደ ሌሎች ሁሉ ይከማቻሉ፤ እንደ እሸትም ራስ ይቈረጣሉ።
25. እንዲህስ ባይሆን ሐሰተኛ የሚያደርገኝ፥ ነገሬንስ እንደ ምናምን የሚያደርገው ማን ነው?

  Job (24/42)