Job (19/42)  

1. ኢዮብም መለሰ እንዲህም አለ።
2. ነፍሴን የምትነዘንዙ፥ በቃልስ የምታደቅቁኝ እስከ መቼ ነው?
3. ይኸው ስትሰድቡኝ አሥር ጊዜ ነው፤ ስታሻክሩኝም አላፈራችሁም።
4. በእውነትም የሳትሁ እንደ ሆነ፥ ስሕተቴ ከእኔ ጋር ትኖራለች።
5. በእውነትም ብትጓደዱብኝ፥ መዋረዴን በእኔ ላይ ብትከራከሩ፥
6. እንግዲህ እግዚአብሔር እንደ ገለበጠኝ፥ በመረቡም እንደ ከበበኝ እወቁ።
7. እነሆ፥ ስለ ተደረገብኝ ግፍ ብጮኽ ማንም አይመልስልኝም፤ አሰምቼም ብጠራ ፍርድ የለኝም።
8. እንዳላልፍ መንገዴን ዘግቶታል፥ በጎዳናዬም ጨለማ አኑሮበታል።
9. ክብሬን ገፈፈኝ፥ ዘውዴንም ከራሴ ላይ ወሰደ።
10. በዚህና በዚያም አፈረሰኝ፥ እኔም ሄድሁ፤ ተስፋዬንም እንደ ዛፍ ነቀለው፤
11. ቍጣውንም አነደደብኝ፥ እንደ ጠላቱም ቈጠረኝ።
12. ሠራዊቱ አብረው መጡ፥ መንገዳቸውንም በላዬ አዘጋጁ፥ በድንኳኔም ዙሪያ ሰፈሩ።
13. ወንድሞቼን ከእኔ ዘንድ አራቀ፥ የሚያውቁኝም አጥብቀው ተለዩኝ።
14. ዘመዶቼ ተቋረጡ፥ ወዳጆቼም ረሱኝ።
15. ቤተ ሰቦቼና ሴቶች ባሪያዎቼ እንደ መጻተኛ ቈጠሩኝ፤ በዓይናቸውም እንደ እንግዳ ሆንሁ።
16. ባሪያዬን ብጠራ፥ በአፌም ባቈላምጥ አይመልስልኝም።
17. ሚስቴ እስትንፋሴን ጠላች፥ የእናቴም ማኅፀን ልጆች ልመናዬን ጠሉ።
18. ሕፃናቶች እንኳ አጠቁኝ፤ ብነሣም በእኔ ላይ ይናገራሉ።
19. አማካሪዎቼ ሁሉ ተጸየፉኝ፤ እኔ የምወድዳቸው በላዬ ተገለበጡ።
20. አጥንቴ ከቁርበቴና ከሥጋዬ ጋር ተጣበቀ፤ ድድ ብቻ ቀርቶልኝ አመለጥሁ።
21. እናንተ ወዳጆቼ ሆይ፥ ማሩኝ፤ የእግዚአብሔር እጅ መትታኛለችና ማሩኝ።
22. ስለ ምን እናንተ እንደ እግዚአብሔር ታሳድዱኛላችሁ? ከሥጋዬስ ስለ ምን አትጠግቡም?
23. ምነው አሁን ቃሌ ቢጻፍ! ምነው በመጽሐፍ ውስጥ ቢታተም!
24. ምነው በብረት ብርና በእርሳስ በዓለቱ ላይ ለዘላለም ቢቀረጽ!
25. እኔን ግን የሚቤዠኝ ሕያው እንደ ሆነ፥ በመጨረሻም ዘመን በምድር ላይ እንዲቆም፥
26. ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ፥ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ።
27. እኔ ራሴ አየዋለሁ፥ ዓይኖቼም ይመለከቱታል፥ ከእኔም ሌላ አይደለም። ልቤ በመናፈቅ ዝሎአል።
28. በእውነት። እንዴት እናሳድደዋለን? የነገሩ ሥር በእርሱ ዘንድ ተገኝቶአል ብትሉ፥
29. ፍርድ እንዳለ ታውቁ ዘንድ ቍጣ የሰይፍን ቅጣት ያመጣልና ከሰይፍ ፍሩ።

  Job (19/42)