Job (17/42)  

1. መንፈሴ ደከመ፥ ዘመኔ አለቀ፥ መቃብርም ተዘጋጅቶልኛል።
2. አላጋጮች በእኔ ዘንድ አሉ፥ ዓይኔም በማስቈጣታቸው አደረች።
3. አሁንም አንተ መያዣ ሆነህ ተዋሰኝ፤ ከእኔ ጋር አጋና የሚመታ ማን ነው?
4. ልባቸውም እንዳያስተውል ከልክለኸዋል፤ ስለዚህ ከፍ ከፍ አታደርጋቸውም።
5. ለብዝበዛ ባልንጀሮቹን አሳልፎ የሚሰጥ ሰው፥ የልጆቹ ዓይን ይጨልማል።
6. ለሕዝብም ምሳሌ አደረገኝ፤ በፊቱ ላይ ጺቅ እንደሚሉበት ሰው ሆንሁ።
7. ዓይኔም ከኀዘን የተነሣ ፈዘዘች፥ ብልቶቼም ሁሉ እንደ ጥላ ሆኑ።
8. ቅኖች ሰዎች በዚህ ነገር ይደነቃሉ፥ ንጹሕም በዝንጉው ላይ ይበሳጫል።
9. ጻድቅ ግን መንገዱን ያጠነክራል፥ እጁም ንጹሕ የሆነ ሰው ኃይልን እየጨመረ ይሄዳል።
10. ነገር ግን እናንተ ሁሉ ተመልሳችሁ ወደ እኔ ኑ፤ በእናንተም ዘንድ ብልሃተኛ አላገኝም።
11. ዕድሜዬ አለፈች፤ አሳቤና የልቤ መሣርያ ተቈረጠ።
12. ሌሊቱን ወደ ቀን ይለውጣሉ፤ ብርሃኑም ወደ ጨለማ የቀረበ ይመስላቸዋል።
13. ተስፋ ባደርግ ሲኦል ቤቴ ናት፤ ምንጣፌንም በጨለማ ዘርግቻለሁ።
14. መበስበስን። አንተ አባቴ ነህ፤ ትልንም። አንቺ እናቴ እኅቴም ነሽ ብያለሁ።
15. እንግዲህ ተስፋዬ ወዴት ነው? ተስፋዬንስ የሚያይ ማን ነው?
16. አብረን በመሬት ውስጥ ስናርፍ፥ ወደ ሲኦል ይወርዳል።

  Job (17/42)