Job (13/42)  

1. እነሆ፥ ይህን ሁሉ ዓይኔ አየች፤ ጆሮዬም ሰምታ አስተዋለችው።
2. እናንተ የምታውቁትን እኔ ደግሞ አውቃለሁ፤ ከእናንተ የማንስ አይደለሁም።
3. ነገር ግን ሁሉን ለሚችል አምላክ መናገር እፈልጋለሁ፥ ከእግዚአብሔርም ጋር ለመዋቀስ እሻለሁ።
4. እናንተ ግን በሐሰት ለባጮች ናችሁ፤ ሁላችሁ የማትጠቅሙ ባለ መድኃኒቶች ናችሁ።
5. ምነው ዝም ብላችሁ ብትኖሩ! ይህ ጥበብ በሆነላችሁ ነበር።
6. አሁንም ክርክሬን ስሙ፥ የከንፈሬንም ሙግት አድምጡ።
7. በውኑ ስለ እግዚአብሔር ሐሰትን ትናገራላችሁን? ስለ እርሱም ሽንገላን ታወራላችሁን?
8. ለፊቱስ ታደላላችሁን? ስለ እግዚአብሔርስ ትከራከራላችሁን?
9. ቢመረምራችሁስ መልካም ይሆንልችኋልን? ወይስ በሰው እንደምትሳለቁ ትሳለቁበታላችሁን?
10. በስውር ለሰው ፊት ብታደሉ ዘለፋ ይዘልፋችኋል።
11. ክብሩስ አያስፈራችሁምን? ግርማውስ አይወድቅባችሁምን?
12. ምስሌዎቻችሁ የአመድ ምሳሌዎች ናቸው፤ ምሽጎቻችሁ የጭቃ ምሽጎች ናቸው።
13. ዝም በሉ፥ እናገርም ዘንድ ተዉኝ፤ የሆነው ነገር ይምጣብኝ።
14. ሥጋዬን በጥርሴ እይዛለሁ፥ ሕይወቴንም በእጄ አኖራለሁ።
15. እነሆ፥ ቢገድለኝ ስንኳ እርሱን በትዕግሥት እጠባበቃለሁ፤ ነገር ግን መንገዴን በፊቱ አጸናለሁ።
16. ዝንጉ ሰው በፊቱ አይገባምና እርሱ መድኃኒት ይሆንልኛል።
17. ነገሬን ተግታችሁ ስሙ፥ ምስክርነቴንም በጆሮአችሁ አድምጡ።
18. እነሆ፥ ሙግቴን አዘጋጅቻለሁ። እንደምጸድቅም አውቃለሁ።
19. ከእኔስ ጋር የሚፋረድ ማን ነው? አሁን እኔ ዝም ብል እሞታለሁ።
20. ነገር ግን ሁለት ነገር አታድርግብኝ፤ የዚያን ጊዜ ከፊትህ አልሰወርም፤
21. እጅህን ከእኔ አርቅ፤ ግርማህም አታስደንግጠኝ።
22. ከዚያም በኋላ ጥራኝ፥ እኔም እመልስልሃለሁ። ወይም እኔ ልናገር፥ አንተም መልስልኝ።
23. ያለብኝስ በደልና ኃጢአት ምን ያህል ነው? መተላለፌንና ኃጢአቴን አስታውቀኝ።
24. ፊትህን ከእኔ የሰወርህ፥ እንደ ጠላትህም የቈጠርኸኝ ስለ ምን ነው?
25. የረገፈውን ቅጠል ታስጨንቃለህን? ወይስ የደረቀውን ዕብቅ ታሳድዳለህን?
26. የመረረ ነገር ጽፈህብኛልና፤ የሕፃንነቴንም ኃጢአት ታወርሰኛለህ።
27. እግሬንም በእግር ግንድ አግብተሃል፥ መንገዴንም ሁሉ መርምረሃል፤ የእግሬን ፍለጋ ወስነሃል።
28. እኔ እንደሚጠፋ በስባሳ ነገር፥ ብልም እንደሚበላው ልብስ ነኝ።

  Job (13/42)