Job (10/42)  

1. ነፍሴ ሕይወቴን ሰለቸቻት፤ የኀዘን እንጕርጕሮዬን እለቀዋለሁ፤ በነፍሴም ምሬት እናገራለሁ።
2. እግዚአብሔርን እንዲህ እለዋለሁ። አትፍረድብኝ፤ የምትከራከረኝ ለምን እንደ ሆነ ንገረኝ።
3. ልታስጨንቅና የእጅህን ሥራ ልትንቅ የኃጥአንንስ ምክር ልታበራ በአንተ ዘንድ መልካም ነውን?
4. በውኑ የሥጋ ዓይን አለህን? ወይስ ሰው እንደሚያይ ታያለህን?
6. ወይስ ክፋቴን ትፈላለግ ዘንድ፥ ኃጢአቴንም ትመረምር ዘንድ፥ ዘመንህ እንደ ሰው ዘመን ነውን? ወይስ ዓመታትህ እንደ ሰው ዓመታት ናቸውን?
7. ከዚህም በላይ በደለኛ እንዳልሆንሁ፥ ከእጅህም የሚያድን እንደሌለ አንተ ታውቃለህ።
8. እጅህ ለወሰችኝ ሠራችኝም፤ ከዚያም በኋላ ዞረህ ታጠፋኝ ዘንድ ፈለግህ።
9. እንደ ጭቃ አድርገህ እንደ ለወስኸኝ አስብ፤ ወደ ትቢያም ትመልሰኛለህን?
10. በውኑ እንደ ወተት አላፈሰስኸኝምን? እንደ እርጎስ አላረጋኸኝምን?
11. ቁርበትና ሥጋ አለበስኸኝ፥ በአጥንትና በጅማትም አጠንከርኸኝ።
12. ሕይወትና ቸርነት አደረግህልኝ፤ መጐብኘትህም መንፈሴን ጠበቀች።
13. እነዚህንም ነገሮች በልብህ ውስጥ ሰወርህ። ይህ ሁሉ በአሳብህ እንዳለ አውቃለሁ።
14. ኃጢአት ብሠራ አንተ ትመለከተኛለህ፤ ከኃጢአቴም ንጹሕ አታደርገኝም።
15. በደለኛ ብሆን ወዮልኝ፤ ጻድቅም ብሆን ራሴን አላነሣም፤ ጕስቍልናን ተሞልቻለሁ፥ መከራዬንም ተመልክቻለሁ።
16. ራሴም ከፍ ከፍ ቢል እንደ አንበሳ ታድነኛለህ፤ ተመልሰህም ድንቅ ነገር ታድርግብኛለህ
17. ምስክሮችህን ታድስብኛለህ፤ ቍጣህንም ታበዛብኛለህ፤ ጭፍራ በጭፍራ ላይ ትጨምርብኛለህ።
18. ስለ ምን ከማኅፀን አወጣኸኝ? ዓይን ሳያየኝ ምነው በሞትሁ።
19. እንዳልነበረ በሆንሁ፤ ከማኅፀንም ወደ መቃብር በወሰዱኝ።
20. የሕይወቴ ዘመን ጥቂት አይደለምን?
21. ወደማልመለስበት ስፍራ፥ ወደ ጨለማና ወደ ሞት ጥላ ምድር፥
22. እንደ ጨለማም ወደ ጨለመች፥ ሥርዓትም ወደሌለባት ወደ ሞት ጥላ፥ ብርሃንዋም እንደ ጨለማ ወደ ሆነ ምድር ሳልሄድ፥ ጥቂት እጽናና ዘንድ ተወኝ፥ ልቀቀኝም።

  Job (10/42)