Isaiah (33/66)  

1. አንተ ሳትጠፋ የምታጠፋ፥ በአንተም ላይ ወንጀል ሳይደረግ ወንጀል የምታደርግ ወዮልህ! ማጥፋትን በተውህ ጊዜ ትጠፋለህ፤ መወንጀልንም በተውህ ጊዜ ይወነጅሉሃል።
2. አቤቱ፥ ማረን፤ አንተን ተማምነናል፤ ጥዋት ጥዋት ክንድ በመከራም ጊዜ ማዳን ሁነን።
3. ከፍጅት ድምፅ ወገኖች ሸሹ፥ በመነሣትህም አሕዛብ ተበተኑ።
4. አንበጣ እንደሚሰበስብ ምርኮአችሁ ትሰበሰባለች፥ ኩብኩባም እንደሚዘልል ሰዎች ይዘልሉበታል።
5. እግዚአብሔር በአርያም ተቀምጦአልና ከፍ ከፍ አለ፤ ጽዮንን በፍርድና በጽድቅ ሞላት።
6. የዘመንህም ጸጥታ፥ የመድኃኒት ብዛት፥ ጥበብና እውቀት ይሆናል፤ እግዚአብሔርን መፍራት መዝገቡ ነው።
7. እነሆ፥ ኃይለኞቻቸው በሜዳ ይጮኻሉ፤ የሰላም መልእክተኞች መራራ ልቅሶ ያለቅሳሉ።
8. መንገዶች ባድማ ሆኑ፥ ተላላፊም ቀረ፤ እርሱም ቃል ኪዳንን አፈረሰ ከተሞችንም ናቀ ሰውንም አልተመለከተም።
9. ምድሪቱ አለቀሰች ከሳችም፤ ሊባኖስ አፈረ ጠወለገም፤ ሳሮን እንደ ምድረ በዳ ሆነ፤ ባሳንና ቀርሜሎስ ቅጠላቸውን አረገፉ።
10. አሁን እነሣለሁ ይላል እግዚአብሔር፤ አሁን እከበራለሁ፤ አሁን ከፍ ከፍ እላለሁ።
11. ገለባን ትፀንሳላችሁ፥ እብቅንም ትወልዳላችሁ፤ እስትንፋሳችሁ የምትበላችሁ እሳት ናት።
12. አሕዛብም እንደ ተቃጠለ ኖራ፥ ተቈርጦም በእሳት እንደ ተቃጠለ እሾህ ይሆናሉ።
13. እናንተ በሩቅ ያላችሁ የሠራሁትን ስሙ፥ እናንተም በቅርብ ያላችሁ ኃይሌን እወቁ።
14. በጽዮን ያሉ ኃጢአተኞች ፈሩ፤ መንቀጥቀጥ ዝንጉዎቹን ያዘ፤ ከምትበላ እሳት ጋር መኖርን የሚችል ከእኛ ማን አለ? ለዘላለምም ከምትነድድ እሳት ጋር መኖርን የሚችል ከእኛ ማን አለ?
15. በጽድቅ የሚሄድ ቅን ነገርንም የሚናገር፥ በሽንገላ የሚገኝ ትርፍን የሚንቅ፥ መማለጃን ከመጨበጥ እጁን የሚያራግፍ፥ ደም ማፍሰስን ከመስማት ጆሮቹን የሚያደነቍር፥ ክፋትንም ከማየት ዓይኖቹን የሚጨፍን ነው።
16. እርሱ ከፍ ባለ ስፍራ ይቀመጣል፤ ጠንካራ አምባ መጠጊያው ይሆናል፤ እንጀራም ይሰጠዋል፥ ውኃውም የታመነች ትሆናለች።
17. ዓይኖችህ ንጉሥን በውበቱ ያዩታል፤ እነርሱም በሩቅ ያለች ምድርን ያዩአታል።
18. ልብህም። ጸሐፊ ወዴት አለ? መዛኝስ ወዴት አለ? ግንቦቹንስ የቈጠረ ወዴት አለ? ብሎ የሚያስፈራ ነገር ያስባል።
19. ጨካኝን ሕዝብ፥ ቋንቋው ለማስተዋል ጥልቅ የሆነውንና አንደበቱ ለማስተዋል ጸያፍ የሆነውን ሕዝብ፥ አታይም።
20. የበዓላችንን ከተማ ጽዮንን ተመልከት፤ ዓይኖችህ የሰላም ማደሪያ፥ ካስማውም ለዘላለም የማይነቀል አውታሩም ሁሉ የማይበጠስ፥ የማይወገድ ድንኳን የሆነውን ኢየሩሳሌምን ያያሉ።
21. እግዚአብሔር በዚያ የሰፉ ወንዞችና የመስኖች ስፍራ ሆኖ ከእኛ ጋር በግርማ ይሆናል፤ የሚቀዘፉ መርከቦች አይገቡባትም፥ ታላላቆችም መርከቦች አያልፉባትም።
22. እግዚአብሔር ፈራጃችን ነው፥ እግዚአብሔር ሕግን ሰጪያችን ነው፥ እግዚአብሔር ንጉሣችን ነው፤ እርሱ ያድነናል።
23. ገመዶችህ ላልተዋል፥ ደቀላቸውንም አላጸኑም፥ ሸራውንም መዘርጋት አልቻሉም። በዚያም ጊዜ የብዙ ምርኮ ብዝበዛ ተከፈለ፤ አንካሶች እንኳ ብዝበዛውን በዘበዙ።
24. በዚያም የሚቀመጥ። ታምሜአለሁ አይልም፥ በእርስዋም ለሚቀመጡ ሰዎች በደላቸው ይቅር ይባልላቸዋል።

  Isaiah (33/66)