Isaiah (10/66)  

2. መበለቶችም ቅሚያቸው እንዲሆኑ፥ ድሀ አደጎችንም ብዝበዛቸው እንዲያደርጉ፥ የድሀውን ፍርድ ያጣምሙ ዘንድ፥ የችግረኛውንም ሕዝቤን ፍርድ ያጐድሉ ዘንድ የግፍን ትእዛዛት ለሚያዝዙ፥ ክፉንም ጽሕፈት ለሚጽፉ ወዮላቸው!
3. በተጎበኛችሁበት ቀን፥ መከራም ከሩቅ በሚመጣበት ዘመን ምን ታደርጉ ይሆን? ለረድኤትስ ወደ ማን ትሸሻላችሁ? ክብራችሁንስ ወዴት ትተዉታላችሁ?
4. ከእስረኞች በታች ይጐነበሳሉ፥ ከተገደሉትም በታች ይወድቃሉ። በዚህም ሁሉ እንኳ ቍጣው አልተመለሰችም፥ ነገር ግን እጁ ገና ተዘርግታ ትኖራለች።
5. ለቍጣዬ በትር ለሆነ፥ የመዓቴም ጨንገር በእጁ ላለ ለአሦር ወዮለት!
6. እርሱንም በዝንጉ ሕዝብ ላይ እልካለሁ፥ ምርኮውንና ብዝበዛውንም ይወስድ ዘንድ እንደ አደባባይም ጭቃ የተረገጡ ያደርጋቸው ዘንድ በምቈጣቸው ሰዎች ላይ አዝዘዋለሁ።
7. እርሱ እንዲሁ አያስብም፥ በልቡም እንዲህ አይመስለውም፤ ነገር ግን ማጥፋት፥ ጥቂት ያይደሉትንም አሕዛብን መቍረጥ በልቡ አለ።
8. እንዲህ ይላል። መሳፍንቴ ሁሉ ነገሥታት አይደሉምን? ካልኖ እንደ ከርከሚሽ አይደለችምን?
9. ሐማትስ እንደ አርፋድ አይደለችምን? ሰማርያስ እንደ ደማስቆ አይደለችምን?
10. የተቀረጹ ምስሎቻቸው ከኢየሩሳሌምና ከሰማርያ ምስሎች የበለጡትን የጣዖቶችን መንግሥታት እጄ እንዳገኘች፥
11. በሰማርያና በጣዖቶችዋም እንዳደረግሁ፥ እንዲሁስ በኢየሩሳሌምና በጣዖቶችዋ አላደርግምን?
12. ስለዚህ እንዲህ ይሆናል፤ ጌታ ሥራውን ሁሉ በጽዮን ተራራና በኢየሩሳሌም ላይ በፈጸመ ጊዜ የአሦርን ንጉሥ የኩሩ ልብ ፍሬን የዓይኑንም ከፍታ ትምክሕት ይጐበኛል።
13. እርሱ እንዲህ ብሎአልና። አስተዋይ ነኝና በእጄ ኃይልና በጥበቤ አደረግሁት፤ የአሕዛብን ድንበሮች አራቅሁ፥ ሀብታቸውንም ዘረፍሁ፥ እንደ ጀግናም ሆኜ በምድር የተቀመጡትን አዋረድሁ፤
14. እጄም የአሕዛብን ኃይል እንደ ወፍ ቤት አገኘች፤ የተተወም እንቍላል እንደሚሰበሰብ እንዲሁ እኔ ምድርን ሁሉ ሰበሰብሁ፤ ክንፉን የሚያራግብ አፉንም የሚከፍት የሚጮኽም የለም።
15. በውኑ መጥረቢያ በሚቈርጥበት ሰው ላይ ይመካልን? ወይስ መጋዝ በሚስበው ላይ ይጓደዳልን? ይህስ፥ በትር የሚያነሣውን እንደ መነቅነቅ ዘንግም እንጨት ያይደለውን እንደ ማንሣት ያህል ነው።
16. ስለዚህም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በወፍራሞች ላይ ክሳትን ይልካል፤ ከክብሩም በታች ቃጠሎው እንደ እሳት መቃጠል ይነድዳል።
17. የእስራኤልም ብርሃን እንደ እሳት ቅዱስም እንደ ነበልባል ይሆናል፤ እሾሁንና ኵርንችቱን በአንድ ቀን ያቃጥላል ይበላውማል።
18. ከነፍስም እስከ ሥጋ ድረስ የዱሩንና የሚያፈራውን እርሻ ክብር ይበላል፤ ይህም የታመመ ሰው እንደሚሰለስል ይሆናል።
19. የቀሩትም የዱር ዛፎች በቍጥር ጥቂት ይሆናሉ፥ ታናሽ ብላቴናም ይጽፋቸው ዘንድ ይችላል። v
20. በዚያም ቀን እንዲህ ይሆናል፤ የእስራኤል ቅሬታ ከያዕቆብም ቤት የዳኑት ከእንግዲህ ወዲህ በመቱአቸው ላይ አይደገፉም፤ ነገር ግን በእስራኤል ቅዱስ በእግዚአብሔር ላይ በእውነት ይደገፋሉ።
21. የያዕቆብም ቅሬታ ወደ ኃያል አምላክ ይምለሳሉ።
22. እስራኤል ሆይ፥ የሕዝብህ ቍጥር እንደ ባሕር አሸዋ ቢሆን ቅሬታው ይመለሳል። ጽድቅ የተትረፈረፈበትም ጥፋት ተወስኖአል።
23. የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔርም ያለቀ የተቈረጠ ነገርን በምድር ሁሉ መካከል ይፈጽማል።
24. ስለዚህ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በጽዮን የምትኖር ሕዝቤ ሆይ፥ አሦር በበትር ቢመታህ፥ ግብጽም እንዳደረገ ዘንጉን ቢያነሣብህ አትፍራው።
25. ቍጣዬ እስኪፈጸም መዓቴም እስኪያጠፋቸው ድረስ ጥቂት ጊዜ ቀርቶአልና።
26. የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔርም ምድያምን በሔሬብ ዓለት በኩል እንደ መታው ጅራፍ ያነሣበታል፤ በትሩም በባሕር ላይ ይሆናል፥ በግብጽም እንዳደረገ ያነሣዋል።
27. በዚያም ቀን ሸክሙ ከጫንቃህ ቀንበሩም ከአንገትህ ላይ ይወርዳል፤ ቀንበሩም ከውፍረት የተነሣ ይሰበራል።
28. ወደ አንጋይ መጥቶአል፤ በመጌዶን በኩል አልፎአል፤ በማክማስ ውስጥ ዕቃውን አኑሮአል፤
29. በመተላለፊያ አልፎአል፤ በጌባ ማደሪያው ነው፤ ራማ ደንግጣለች፤ የሳኦል ጊብዓ ኰብልላለች።
30. አንቺ የጋሊም ልጅ ሆይ፥ በታላቅ ድምፅሽ ጩኺ፤ ላይሳ ሆይ፥ አድምጪ፤ ዓናቶት ሆይ፥ መልሽላት።
31. መደቤና ሸሽታለች፤ በግቤርም የሚኖሩ ቤተ ሰቦቻቸውን አሽሽተዋል።
32. ዛሬ በኖብ ይቆማል፤ በጽዮን ሴት ልጅ ተራራ በኢየሩሳሌም ኮረብታ ላይ እጁን ያንቀሳቅሳል።
33. እነሆ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ቅርንጫፎቹን በሚያስፈራ ኃይል ይቈርጣል፤ በቁመት የረዘሙትም ይቈረጣሉ፥ ከፍ ያሉትም ይዋረዳሉ።
34. ጭፍቅ የሆነውንም ዱር በብረት ይቈርጣል፥ ሊባኖስም በኃያሉ እጅ ይወድቃል።

  Isaiah (10/66)