Genesis (43/50)  

2. ራብም በምድር ጸና። ከግብፅም ያመጡትን እህል በልተው ከፈጸሙ በኋላ አባታቸው። እንደ ገና ሂዱ፤ ጥቂት እህል ሸምቱልን አላቸው።
3. ይሁዳም እንዲህ አለው። ያ ሰው። ወንድማችሁ ከእናንተ ጋር ካልሆነ ፊቴን አታዩም ብሎ በብርቱ ቃል አስጠነቀቀን።
4. ወንድማችንን ከእኛ ጋር ብትሰድደው እንወርዳለን፥ እህልም እንሸምትልሃለን፤
5. ባትሰድደው ግን አንሄድም፤ ያ ሰው። ወንድማችሁ ከእናንተ ጋር ካልሆነ ፊቴን አታዩም ብሎናልና።
6. እስራኤልም አላቸው። ለምን በደላችሁኝ? ለዚያውስ። ሌላ ወንድም አለን ብላችሁ ለምን ነገራችሁት?
7. እነርሱም አሉ። ያ ሰው ስለ እኛና ስለ ወገናችን ፈጽሞ ጠየቀን እንዲህም አለን። አባታችሁ ገና በሕይወት ነው? ወንድምስ አላችሁን? እኛም እንደዚሁ እንደ ጥያቄው መለስንለት፤ በውኑ። ወንድማችሁን አምጡ እንዲለን እናውቅ ነበርነን?
8. ይሁዳም አባቱን እስራኤልን አለው። እኛና አንተ ልጆቻችንም ደግሞ እንድንድን እንዳንሞትም ብላቴናውን ከእኔ ጋር ስደደው፥ እኛም ተነሥተን እንሄዳለን።
9. እኔ ስለ እርሱ እዋሳለሁ ከእጄ ትሻዋለህ፤ ወደ አንተ ባላመጣው፥ በፊትህም ባላቆመው፥ በዘመናት ሁሉ አንተን የበደልሁ ልሁን።
10. ባንዘገይስ ኖሮ አሁን ሁለተኛ ጊዜ በተመለስን ነበር።
11. እስራኤልም አባታቸው እንዲህ አላቸው። ነገሩ እንዲህ ከሆነስ ይህንን አድርጉ፤ ከተመሰገነው ከምድሩ ፍሬ በዓይበታችሁ ይዛችሁ ሂዱ፥ ለዚያም ሰው እጅ መንሻ፥ ጥቂት በለሳን፥ ጥቂት ማር፥ ሽቱ፥ ከርቤ፥ ተምር፥ ለውዝ ውሰዱ።
12. ብሩን በአጠፌታ አድርጋችሁ በእጃችሁ ውሰዱ፤ በዓይበታችሁ አፍ የተመለሰውንም ብር መልሳችሁ ውሰዱ፤ ምናልባት በስሕተት ይሆናል።
13. ወንድማችሁንም ውሰዱ፥ ተነሥታችሁም ወደዚያ ሰው ተመለሱ።
14. ሁሉን የሚችል አምላክም ሌላውን ወንድማችሁንና ብንያምን ከእናንተ ጋር ይሰድድ ዘንድ በዚያ ሰው ፊት ምሕረትን ይስጣችሁ፤ እኔም ልጆቼን እንዳጣሁ አጣሁ።
15. ሰዎቹም በእጃቸው ያችን እጅ መንሻና አጠፌታውን ብር ብንያምንም ወሰዱ፤ ተነሥተውም ወደ ግብፅ ወረዱ፥ በዮሴፍም ፊት ቆሙ።
16. ዮሴፍም ብንያምን ከእነርሱ ጋር ባየው ጊዜ የቤቱን አዛዥ እንዲህ ብሎ አዘዘው። እነዚያን ሰዎች ወደ ቤት አስገባቸው፥ እርድም እረድ አዘጋጅም፥ እነዚያ ሰዎች በእኩለ ቀን ከእኔ ጋር ይበላሉና።
17. ያ ሰውም ዮሴፍ እንዳለው አደረገ፤ ያ ሰውም ሰዎቹን ወደ ዮሴፍ ቤት አስገባ።
18. እነርሱም ወደ ዮሴፍ ቤት ስለ ገቡ ፈሩ፤ እንዲህም አሉ። በዓይበታችን ቀድሞ ስለ ተመለሰው ብር ሊተነኰልብን ሊወድቅብንም፥ እኛንም በባርነት ሊገዛ አህዮቻችንንም ሊወስድ ወደዚህ አስገባን።
19. ወደ ዮሴፍ ቤት አዛዥም ቀረቡ፥ በቤቱም ደጅ ተናገሩት፥
20. እንዲህም አሉት። ጌታዬ ሆይ፥ ቀድሞ እህልን ልንሸምት ወርደን ነበር፤
21. ወደምናድርበትም ስፍራ በደረስን ጊዜ ዓይበታችንን ከፈትን፥ እነሆም፥ የእያንዳንዱ ሰው ብር በየዓይበቱ አፍ እንደ ሚዛኑ ብራችን ነበረ፤ አሁንም በእጃችን መለስነው።
22. እህል እንሸምትበት ዘንድ ሌላም ብር በእጃችን አመጣን፤ ብራችንንም በዓይበታችን ማን እንደ ጨመረው አናውቅም።
23. እርሱም አላቸው። ሰላም ለእናንተ ይሁን፥ አትፍሩ፤ አምላካችሁና የአባታችሁ አምላክ በዓይበታችሁ የተሰወረ ገንዘብ ሰጣችሁ፤ ብራችሁስ ደርሶኛል።
24. ስምዖንንም አወጣላቸው። ሰውዮውም እነዚያን ስዎች ወደ ዮሴፍ ቤት አስገባቸው፤ ውኃ አመጣላቸው፥ እግራቸውንም ታጠቡ፤ ለአህዮቻቸው አበቅ ሰጣቸው።
25. ዮሴፍም በእኩለ ቀን እስኪገባ ድረስ እነርሱ እጅ መንሻቸውን አዘጋጁ፥ ከዚያ እንጀራን እንደሚበሉ ሰምተዋልና።
26. ዮሴፍም ወደ ቤቱ በገባ ጊዜ በእጃቸው ያለውን እጅ መንሻ በቤት ውስጥ አቀረቡለት፥ ወደ ምድርም ወድቀው ሰገዱለት።
27. እርሱም ደኅንነታቸውን ጠየቃቸው፥ እንዲህም አለ። የነገራችሁኝ ሽማግሌ አባታችሁ ደኅና ነውን? ገና በሕይወት አለን?
28. እነርሱም አሉት። ባሪያህ አባታችን ደኅና ነው፤ ገና በሕይወት አለ። አጐንብሰውም ሰገዱለት።
29. ዓይኑንም አንሥቶ የእናቱን ልጅ ብንያምን አየው፥ እርሱም አለ። የነገራችሁኝ ታናሽ ወንድማችሁ ይህ ነውን? እንዲህም አለው። ልጄ ሆይ፥ እግዚአብሔር ይባርክህ።
30. ዮሴፍም ቸኮለ፥ አንጀቱ ወንድሙን ናፍቆታልና፤ ሊያለቅስም ወደደ፤ ወደ እልፍኙም ገብቶ ከዚያ አለቀሰ።
31. ፊቱንም ታጥቦ ወጣ፥ ልቡንም አስታግሦ። እንጀራ አቅርቡ አለ።
32. ለእርሱም ለብቻው አቀረቡ፥ ለእነርሱም ለብቻቸው፥ ከእርሱ ጋር ለሚበሉት ለግብፅ ሰዎችም ለብቻቸው፤ የግብፅ ሰዎች ከዕብራውያን ጋር መብላት አይሆንላቸውምና፥ ይህ ለግብፅ ሰዎች እንደ መርከስ ነውና።
33. በፊቱም በኵሩ እንደ ታላቅነቱ ታናሹም እንደ ታናሽነቱ ተቀመጡ፤ ሰዎቹም እርስ በርሳቸው ተደነቁ።
34. በፊቱም ካለው መብል ፈንታቸውን አቀረበላቸው፤ የብንያምም ፈንታ ከሁሉ አምስት እጅ የሚበልጥ ነበረ። እነርሱም ጠጡ ከእርሱም ጋር ደስ አላቸው።

  Genesis (43/50)