Genesis (29/50)  

1. ያዕቆብም ተነሥቶ ወደ ምሥራቅ ሰዎች አገር ሄደ።
2. በሜዳውም እነሆ ጕድጓድን አየ፥ በዚያም ሦስት የበጎች መንጎች በላዩ ተመስገው ነበር፤ ከዚያ ጕድጓድ በጎቹን ያጠጡ ነበርና፤ በጕድጓዱም አፍ የነበረው ድንጋይ ትልቅ ነበረ።
3. መንጎችም ሁሉ ከዚያ በተከማቹ ጊዜ ድንጋዩን ከጕድጓዱ አፍ ገለል አድርገው በጎቹን ያጠጡ ነበር፤ ድንጋዩንም ወደ ስፍራው መልሰው በጕድጓዱ አፍ እንደ ገና ይገጥሙት ነበር።
4. ያዕቆብም። ወንድሞቼ ሆይ፥ እናንት የወዴት ናችሁ? አላቸው። እነርሱም። እኛ የካራን ነን አሉት።
5. የናኮርን ልጅ ላባን ታውቁታላችሁን? አላቸው። እነርሱም። እናውቀዋለን አሉት።
6. እርሱ። ደኅና ነውን? አላቸው። እነርሱም። አዎን ደኅና ነው፤ አሁንም ልጁ ራሔል ከበጎች ጋር መጣች አሉት።
7. እርሱም። ቀኑ ገና ቀትር ነው፥ ከብቶቹ የሚከማቹበት ሰዓቱም ገና አልደረሰም፤ አሁንም በጎቹን አጠጡና ሄዳችሁ አሰማሩአቸው አላቸው።
8. እነርሱም አሉ። መንጎች ሁሉ እስኪከማቹና ድንጋዩን ከጕድጓዱ አፍ እስኪገለብጡት ድረስ አንችልም፤ ከዚያም በኋላ በጎቹን እናጠጣለን።
9. እርሱም ገና ከእነርሱ ጋር ሲነጋገር እነሆ የላባ ልጅ ራሔል ከአባትዋ በጎች ጋር ደረሰች፤ እርስዋ የአባትዋን በጎች ትጠብቅ ነበርና።
10. ያዕቆብም የእናቱን ወንድም የላባን ልጅ ራሔልንና የእጎቱን የላባን በጎች ባየ ጊዜ፥ ቀረበ ከጕድጓዱም አፍ ድንጋዩን ገለበጠ፥ የአጎቱን የላባን በጎችንም አጠጣ።
11. ያዕቆብም ራሔልን ሳማት፥ ቃሉንም ከፍ አድርጎ አለቀሰ።
12. ያዕቆብም የአባትዋ ዘመድና የርብቃ ልጅ መሆኑን ለራሔል አስታወቃት፤ እርስዋም ሮጣ ሄዳ ለአባትዋ ይህን ነገር ነገረችው።
13. ላባም የእኅቱን ልጅ የያዕቆብን ወሬ በሰማ ጊዜ ሊቀበለው ሮጠ፥ አቅፎም ሳመው፥ ወደ ቤቱም አገባው። ነገሩንም ሁሉ ለላባ ነገረው ።
14. ላባም። በእውነት አንተ አጥንቴ ሥጋዬም ነህ አለው። አንድ ወር የሚያህልም ከእርሱ ጋር ተቀመጠ።
15. ላባም ያዕቆብን። ወንድሜ ስለሆንህ በከንቱ ታገለግለኛለህን? ምንዳህ ምንድር ነው? ንገረኝ አለው።
16. ለላባም ሁለት ሴቶች ልጆች ነበሩት፤ የታላቂቱ ስም ልያ የታናሺቱ ስም ራሔል ነበረ።
17. ልያም ዓይነ ልም ነበረች፤ ራሔል ግን መልከ መልካም ነበረች ፊትዋም ውብ ነበረ።
18. ያዕቆብም ራሔልን ወደደ፤ እንዲህም አለ። ስለ ታናሺቱ ልጅህ ስለ ራሔል ሰባት ዓመት እገዛልሃለሁ።
19. ላባም። ለሌላ ሰው ከምሰጣት ይልቅ ለአንተ ብሰጣት ይሻላል፤ ከእኔ ጋር ተቀመጥ አለ።
20. ያዕቆብም ስለ ራሔል ሰባት ዓመት ተገዛ፤ እርስዋንም ይወድዳት ስለነበረ በእርሱ ዘንድ እንደ ጥቂት ቀን ሆነለት።
21. ያዕቆብም ላባን። ወደ እርስዋ እገባ ዘንድ ሚስቴን ስጠኝ፥ ቀኔ ተፈጽሞአልና አለው።
22. ላባም የዚያን ስፍራ ሰዎች ሁሉ ሰበሰበ፥ ሰርግም አደረገ።
23. በመሸም ጊዜ ልጁን ልያን ወስዶ ለያዕቆብ አገባለት፤ ያዕቆብም ወደ እርስዋ ገባ።
24. ላባም ለልጁ ለልያ ባሪያይቱን ዘለፋን ባርያ ትሆናት ዘንድ ሰጣት።
25. በነጋም ጊዜ እነሆ ልያ ሆና ተገኘች፤ ላባንም። ምነው እንደዚህ አደረግህብኝ? ያገለገልሁህ ስለ ራሔል አልነበረምን? ለምን አታለልኸኝ? አለው።
26. ላባም እንዲህ አለ። በአገራችን ታላቂቱ ሳለች፥ ታናሺቱን እንሰጥ ዘንድ ወግ አይደለም፤
27. ይህችንም ሳምንት ፈጽም፤ ሌላ ሰባት ዓመት ደግሞ እኔን ስለምታገለግለኝ አገልግሎት እርስዋን ደግሞ እሰጥሃለሁ።
28. ያዕቆብም እንዲህ አደረገ፥ ይህችንም ሳምንት ፈጸመ፤ ልጁን ራሔልንም ለእርሱ ሚስት ትሆን ዘንድ ሰጠው።
29. ላባም ለልጁ ለራሔል ባርያይቱን ባላን ባርያ ትሆናት ዘንድ ሰጣት ።
30. ያዕቆብም ወደ ራሔል ደግሞ ገባ። ራሔልንም ከልያ ይልቅ ወደዳት፤ ሌላ ሰባት ዓመትም ተገዛለት።
31. እግዚአብሔርም ልያ የተጠላች መሆንዋን ባየ ጊዜ ማኅፀንዋን ከፈተላት፤ ራሔል ግን መካን ነበረች።
32. ልያም ፀነሰች፥ ወንድ ልጅንም ወለደች፥ ስሙንም ሮቤል ብላ ጠራችው፤ እግዚአብሔር መከራዬን አይቶአልና፥ እንግዲህም ወዲህ ባሌ ይወድደኛል ብላለችና።
33. ደግሞም ፀነሰች፥ ወንድ ልጅንም ወለደች፤ እኔ እንደ ተጠላሁ እግዚአብሔር ስለ ሰማ ይህን ደገመኝ አለች፤ ስሙንም ስምዖን ብላ ጠራችው።
34. ደግሞም ፀነሰች፥ ወንድ ልጅንም ወለደች፤ አሁንም ባሌ ወደ እኔ ይጠጋል፥ ሦስት ወንዶች ልጆችን ወልጄለታለሁና አለች፤ ስለዚህም ስሙን ሌዊ ብላ ጠራችው።
35. ደግሞም ፀነስች፥ ወንድ ልጅንም ወለደች፤ በዚህም ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ አለች፤ ስለዚህም ስሙን ይሁዳ ብላ ጠራችው። መውለድንም አቆመች።

  Genesis (29/50)