← Ecclesiastes (11/12) → |
1. | እንጀራህን በውኃ ፊት ላይ ጣለው፥ ከብዙ ቀን በኋላ ታገኛዋለህና። |
2. | ለሰባት ደግሞም ለስምንት እድል ፈንታን ክፈል፥ በምድር ላይ የሚሆነውን ክፉ ነገር ምን እንደሆነ አታውቅምና። |
3. | ደመናት ዝናብ በሞሉ ጊዜ በምድር ላይ ያፈስሱታል፤ ዛፍም ወደ ደቡብ ወይም ወደ ሰሜን ቢወድቅ፥ ዛፉ በወደቀበት ስፍራ በዚያ ይኖራል። |
4. | ነፋስን የሚጠባበቅ አይዘራም፥ ደመናንም የሚመለከት አያጭድም። |
5. | የነፋስ መንገድ እንዴት እንደ ሆነች አጥንትም በእርጉዝ ሆድ እንዴት እንድትዋደድ እንደማታውቅ፥ እንዲሁም ሁሉን የሚሠራውን የእግዚአብሔርን ሥራ አታውቅም። |
6. | ወይም ይህ ወይም ያ ማናቸው እንዲበቅል ወይም ሁለቱ መልካም እንዲሆኑ አታውቅምና በማለዳ ዘርህን ዝራ፥ በማታም እጅህን አትተው። |
7. | ብርሃን ጣፋጭ ነው ፀሐይንም ማየት ለዓይን መልካም ነው። |
8. | ሰው ብዙ ዘመን በሕይወት ቢኖር በሁሉም ደስ ይበለው፤ ሆኖም የጨለማውን ዘመን ያስብ፥ ብዙ ቀን ይሆናልና። የሚመጣው ነገር ሁሉ ከንቱ ነው። |
9. | አንተ ጐበዝ፥ በጕብዝናህ ደስ ይበልህ፥ በጕብዝናህም ወራት ልብህን ደስ ይበለው፥ በልብህም መንገድ ዓይኖችህም በሚያዩት ሂድ፤ ዳሩ ግን ስለዚህ ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ወደ ፍርድ እንዲያመጣህ እወቅ። |
10. | ሕፃንነትና ጕብዝና ከንቱዎች ናቸውና ከልብህ ኀዘንን አርቅ፥ ከሰውነትህም ክፉን ነገር አስወግድ። |
← Ecclesiastes (11/12) → |