2Samuel (24/24)    

1. ደግሞም የእግዚአብሔር ቍጣ በእስራኤል ላይ ነደደ፥ ዳዊትንም። ሂድ፥ እስራኤልንና ይሁዳን ቍጠር ብሎ በላያቸው አስነሣው።
2. ንጉሡም ኢዮአብንና ከእርሱ ጋር የነበሩትን የሠራዊት አለቆች። የሕዝቡን ድምር አውቅ ዘንድ ከዳን ጀምሮ እስከ ቤርሳቤህ ድረስ ተመላለሱ፥ ሕዝቡንም ቍጠሩአቸው አላቸው።
3. ኢዮአብም ንጉሡን። የጌታዬ የንጉሡ ዓይን እያየ አምላክህ እግዚአብሔር ዛሬ ካለው ሕዝብ መጠን በላይ መቶ እጥፍ ይጨምርበት፤ ጌታዬ ንጉሡ ግን ይህን ነገር ለምን ይወድዳል? አለው።
4. ነገር ግን የንጉሡ ቃል በኢዮአብና በሠራዊቱ አለቆች ላይ አሸነፈ። ኢዮአብና የሠራዊቱ አለቆችም የእስራኤልን ሕዝብ ይቈጥሩ ዘንድ ከንጉሥ ዘንድ ወጡ።
5. ዮርዳኖስንም ተሻገሩ፤ በጋድ ሸለቆ መካከል ባለችው በኢያዜር ከተማ ቀኝ በኩል በአሮዔር ላይ ሰፈሩ።
6. ወደ ገለዓድም ወደ ተባሶን አዳሰይ አገር መጡ፤ ወደ ዳንየዓንም ደረሱ፥ ወደ ሲዶናም ዞሩ፥
7. ወደ ጢሮስም ምሽግ ወደ ኤዊያውያንና ወደ ከነዓናውያንም ከተሞች ሁሉ መጡ፤ በይሁዳም ደቡብ በኩል በቤርሳቤህ ወጡ።
8. በአገሪቱም ሁሉ ላይ ተመላልሰው ከዘጠኝ ወርና ከሀያ ቀን በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ።
9. ኢዮአብም የሕዝቡን ቁጥር ድምር ለንጉሡ ሰጠ፤ በእስራኤልም ሰይፍ የሚመዝዙ ስምንት መቶ ሺህ ጽኑዓን ሰዎች ነበሩ፤ የይሁዳም ሰዎች አምስት መቶ ሺህ ነበሩ።
10. ሕዝቡንም ከቈጠረ በኋላ ዳዊትን ልቡ መታው፤ ዳዊትም እግዚአብሔርን። ባደረግሁት ነገር እጅግ በድያለሁ፤ አሁን ግን፥ አቤቱ፥ ታላቅ ስንፍና አድርጌአለሁና የባሪያህን ኃጢአት ታርቅ ዘንድ እለምንሃለሁ አለው።
11. ዳዊትም ማልዶ በተነሣ ጊዜ፥ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዳዊት ባለ ራእይ ወደ ነቢዩ ወደ ጋድ እንዲህ ሲል መጣ።
12. ሂድ ለዳዊት። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ሦስት ነገሮች በፊትህ አኖራለሁ፤ አደርግብህ ዘንድ ከእነርሱ አንዱን ምረጥ ብለህ ንገረው አለው።
13. ጋድም ወደ ዳዊት መጥቶ። የሦስት ዓመት ራብ በአገርህ ላይ ይምጣብህን? ወይስ ጠላቶችህ እያሳደዱህ ሦስት ወር ከእነርሱ ትሸሽን? ወይስ የሦስት ቀን ቸነፈር በአገርህ ላይ ይሁን? አሁንም ለላከኝ ምን መልስ እንደምሰጥ አስብና መርምር ብሎ ነገረው።
14. ዳዊትም ጋድን። እጅግ ተጨንቄአለሁ፤ ምሕረቱ ብዙ ነውና በእግዚአብሔር እጅ እንውደቅ፤ በሰው እጅ ግን አልውደቅ አለው።
15. ዳዊትም ቸነፈሩን መረጠ፤ የስንዴም መከር ወራት በሆነ ጊዜ ቸነፈሩ በሕዝቡ መካከል ጀመረ፤ ከሕዝቡም ሰባ ሺህ ሰው ሞተ።
16. የእግዚአብሔርም መልአክ ኢየሩሳሌምን ያጠፋት ዘንድ እጁን በዘረጋ ጊዜ እግዚአብሔር ስለ ክፉው ነገር አዘነ፥ ሕዝቡንም የሚያጠፋውን መልአክ። እንግዲህ በቃህ፤ እጅህን መልስ አለው። የእግዚአብሔርም መልአክ በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ አጠገብ ነበረ።
17. ዳዊትም ሕዝቡን የሚመታውን መልእክ ባየ ጊዜ እግዚአብሔርን። እነሆ፥ እኔ በድያለሁ ጠማማም ሥራ እኔ አድርጌአለሁ፤ እነዚህ በጎች ግን እነርሱ ምን አደረጉ? እጅህ በእኔና በአባቴ ቤት ላይ እንድትሆን እለምንሃለሁ ብሎ ተናገረው።
18. በዚያም ቀን ጋድ ወደ ዳዊት መጥቶ። ውጣ፥ በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሥራ አለው።
19. ዳዊትም እግዚአብሔር እንዳዘዘው እንደ ጋድ ነገር ወጣ።
20. ኦርናም ሲመለከት ንጉሡና ባሪያዎቹ ወደ እርሱ ሲመጡ አየ፤ ኦርናም ወጥቶ በንጉሡ ፊት በምድር ላይ በግምባሩ ተደፋ።
21. ኦርናም። ጌታዬን ንጉሡን ወደ ባሪያው ያመጣው ምክንያት ምንድር ነው? አለ። ዳዊትም። መቅሠፍቱ ከሕዝቡ ላይ ይከለከል ዘንድ አውድማውን ከአንተ ገዝቼ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ልሠራ ነው አለው።
22. ኦርናም ዳዊትን። ጌታዬ ንጉሡ እንደ ወደደ ወስዶ ያቅርብ፤ እነሆ፥ ለሚቃጠል መሥዋዕት በሬዎች፥ ለሚቃጠልም እንጨት የአውድማ ዕቃና የበሬ ቀንበር አለ።
23. ንጉሥ ሆይ፥ ይህን ሁሉ ኦርና ለንጉሡ ይሰጣል አለው፤ ኦርናም ንጉሡን። አምላክህ እግዚአብሔር ይቀበልህ አለው።
24. ንጉሡም ኦርናን። እንዲህ አይደለም፥ ነገር ግን በዋጋ ከአንተ እገዛለሁ፤ ለአምላኬም ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት ያለ ዋጋ አላቀርብም አለው። ዳዊትም አውድማውንና በሬዎቹን በአምሳ ሰቅል ብር ገዛ።
25. በዚያም ዳዊት ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠራ፥ የሚቃጠልና የደኅንነትንም መሥዋዕት አቀረበ። እግዚአብሔርም ስለ አገሪቱ የተለመነውን ሰማ፥ መቅሠፍቱም ከእስራኤል ተከለከለ።

  2Samuel (24/24)