1Samuel (23/31)  

1. ለዳዊትም። እነሆ፥ ፍልስጥኤማውያን ቅዒላን ይወጋሉ፥ አውድማውንም ይዘርፋሉ የሚል ወሬ ደረሰው።
2. ዳዊትም። ልሂድን? እነዚህንስ ፍልስጥኤማውያን ልምታን? ብሎ እግዚአብሔርን ጠየቀ፤ እግዚአብሔርም ዳዊትን። ሂድ፥ ፍልስጥኤማውያንን ምታ ቅዒላንም አድን አለው።
3. የዳዊትም ሰዎች። እነሆ፥ በዚህ በይሁዳ መቀመጥ እንፈራለን፥ ይልቁንስ በፍልስጥኤማውያን ጭፍሮች ላይ ወደ ቅዒላ ብንሄድ እንዴት ነው? አሉት።
4. ዳዊትም ደግሞ እግዚአብሔርን ጠየቀ፤ እግዚአብሔርም መልሶ። ፍልስጥኤማውያንን በእጅህ አሳልፌ እሰጣለሁና ተነሥተህ ወደ ቅዒላ ውረድ አለው።
5. ዳዊትና ሰዎቹም ወደ ቅዒላ ሄዱ፥ ከፍልስጥኤማውያንም ጋር ተዋጉ፤ እንስሶቻቸውንም ማረኩ፥ በታላቅም አገዳደል ገደሉአቸው። ዳዊትም በቅዒላ የሚኖሩትን አዳነ።
6. እንዲህም ሆነ፤ የአቢሜሌክ ልጅ አብያታር ወደ ዳዊት ወደ ቅዒላ በኰበለለ ጊዜ ኤፉዱን ይዞ ወርዶ ነበር።
7. ሳኦልም ዳዊት ወደ ቅዒላ እንደ መጣ ሰማ፤ ሳኦልም። መዝጊያና መወርወሪያ ወዳለባት ከተማ ገብቶ ተገኝቶአልና እግዚአብሔር በእጄ አሳልፎ ሰጥቶታል አለ።
8. ሳኦልም ወደ ቅዒላ ወርደው ይዋጉ ዘንድ፥ ዳዊትንና ሰዎቹንም ይከብቡ ዘንድ ሕዝቡን ሁሉ አዘዘ።
9. ዳዊትም ሳኦል ክፉን እንዳሰበበት አወቀ፤ ካሁኑን አብያታርንም። ኤፉዱን ወደዚህ አምጣ አለው።
10. ዳዊትም። የእስራኤል አምላክ አቤቱ፥ በእኔ ምክንያት ከተማይቱን ያጠፋ ዘንድ ሳኦል ወደ ቅዒላ ሊመጣ እንደሚፈልግ እኔ ባሪያህ ፈጽሜ ሰምቻለሁ።
11. የቅዒላ ሰዎች በእጁ አሳልፈው ይሰጡኛልን? ባሪያህስ እንደ ሰማ ሳኦል በውኑ ይወርዳልን? የእስራኤል አምላክ አቤቱ፥ እንድትነግረኝ እለምንሃለሁ አለ። እግዚአብሔርም። ይወርዳል አለ።
12. ዳዊትም። የቅዒላ ሰዎች እኔንና ሰዎቼን በሳኦል እጅ አሳልፈው ይሰጡናልን? አለ። እግዚአብሔርም። አሳልፈው ይሰጡአችኋል ብሎ ተናገረ።
13. ዳዊትና ስድስት መቶ የሚሆኑ ሰዎችም ተነሥተው ከቅዒላ ወጡ፥ መሄድም ወደሚችሉበት ሄዱ። ሳኦልም ዳዊት ከቅዒላ እንደ ሸሸ ሰማ፤ ስለዚህም ከመውጣት ቀረ።
14. ዳዊትም በምድረ በዳ በአምባ ውስጥ ይኖር ነበር፥ ከዚፍ ምድረ በዳም ባለው በተራራማው አገር ተቀመጠ፤ ሳኦልም ሁልጊዜ ይፈልገው ነበር፥ እግዚአብሔር ግን በእጁ አሳልፎ አልሰጠውም።
15. ዳዊትም ሳኦል ነፍሱን ሊፈልግ እንደ ወጣ አየ፤ ዳዊትም በዚፍ ምድረ በዳ በጥሻው ውስጥ ይኖር ነበር።
16. የሳኦልም ልጅ ዮናታን ተነሥቶ ወደ ዳዊት ወደ ጥሻው ስጥ ሄደ፤ እጁንም በእግዚአብሔር አጽንቶ።
17. የአባቴ የሳኦል እጅ አታገኝህምና አትፍራ፤ አንተም በእስራኤል ላይ ንጉሥ ትሆናለህ፥ እኔም ከአንተ በታች ሁለተኛ እሆናለሁ፤ ይህን ደግሞ አባቴ ሳኦል ያውቃል አለው።
18. ሁለቱም በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አደረጉ፤ ዳዊትም በጥሻው ውስጥ ተቀመጠ፥ ዮናታንም ወደ ቤቱ ሄደ።
19. የዚፍ ሰዎችም ወደ ሳኦል ወደ ጊብዓ መጥተው። እነሆ፥ ዳዊት በየሴሞን ደቡብ በኩል በኤኬላ ኮረብታ ላይ በጥሻ ውስጥ ባሉት አምባዎች በእኛ ዘንድ ተሸሽጎ የለምን?
20. አሁንም፥ ንጉሥ ሆይ፥ ትወርድ ዘንድ ነፍስህ እንደ ወደደች ውረድ፤ በንጉሡም እጅ እርሱን አሳልፎ ለመስጠት እኛ አለን አሉት።
21. ሳኦልም አለ። እናንተ ስለ እኔ አዝናችኋልና ከእግዚአብሔር ዘንድ የተባረካችሁ ሁኑ፤
22. አሁንም ደግሞ ሂዱ፤ እርሱም እጅግ ተንኰለኛ እንደ ሆነ ሰምቻለሁና አጥብቃችሁ ፈልጉት፥ እግሩም የሚሄድበትን ስፍራ እዩና እወቁ፥ በዚያ ያየውንም ሰው አግኙ።
23. እርሱ የሚደበቅበትንና የሚሸሸግበትን ስፍራ እዩና እወቁ፥ በእርግጥም ወደ እኔ ተመለሱ፥ እኔም ከእናንተ ጋር እሄዳለሁ፤ በምድርም ውስጥ ቢሸሸግ በይሁዳ አእላፋት ሁሉ መካከል እፈልገዋለሁ።
24. እነዚያም ተነሥተው ከሳኦል በፊት ወደዚፍ ሄዱ፤ ዳዊትና ሰዎቹ ግን በየሴሞን ደቡብ በኩል በዓረባ በማዖን ምድረ በዳ ነበሩ።
25. ሳኦልና ሰዎቹም ሊፈልጉት ሄዱ፤ ዳዊትም በሰማ ጊዜ ወደ ዓለቱ ወርዶ በማዖን ምድረ በዳ ተቀመጠ፤ ሳኦልም ያንን በሰማ ጊዜ ዳዊትን በማዖን ምድረ በዳ አሳደደው።
26. ሳኦልም በተራራው በአንድ ወገን ሄደ፥ ዳዊትና ሰዎቹም በተራራው በሌላው ወገን ሄዱ። ሳኦልና ሰዎቹም ዳዊትንና ሰዎቹን ለመያዝ ከብበዋቸው ነበርና ዳዊት ከሳኦል ፊት ያመልጥ ዘንድ ፈጠነ።
27. ወደ ሳኦልም መልእክተኛ መጥቶ። ፍልስጥኤማውያን አገሩን ወርረውታልና ፈጥነህ ና አለው።
28. ሳኦልም ዳዊትን ማሳደድ ትቶ ተመለሰ፥ ከፍልስጥኤማውያንም ጋር ሊዋጋ ሄደ። ስለዚህ የዚህ ስፍራ ስም የማምለጥ ዓለት ተባለ።
29. ዳዊትም ከዚያ ወጥቶ በዓይንጋዲ አምባዎች ተቀመጠ።

  1Samuel (23/31)