1Samuel (22/31)  

1. ዳዊትም ከዚያ ተነሣ ወደ ዓዶላም ዋሻ ኮበለለ፤ ወንድሞቹና የአባቱም ቤተ ሰብ ሁሉ ይህን በሰሙ ጊዜ ወደ እርሱ ወደዚያ ወረዱ።
2. የተጨነቀውም ሁሉ፥ ብድርም ያለበት ሁሉ፥ የተከፋም ሁሉ ወደ እርሱ ተከማቸ፤ እርሱም በላያቸው አለቃ ሆነ፤ ከእርሱም ጋር አራት መቶ የሚያህሉ ሰዎች ነበሩ።
3. ዳዊትም ከዚያ በሞዓብ ምድር ወዳለችው ወደ ምጽጳ ሄደ፤ የሞዓብንም ንጉሥ። እግዚአብሔር የሚያደርግልኝን እስካውቅ ድረስ አባቴና እናቴ ከአንተ ጋር ይቀመጡ ዘንድ እለምንሃለሁ አለው።
4. በሞዓብም ንጉሥ ፊት አመጣቸው፤ ዳዊትም በአምባ ውስጥ በነበረበት ወራት ሁሉ በእርሱ ዘንድ ተቀመጡ።
5. ነቢዩ ጋድም ዳዊትን። ተነሥተህ ወደ ይሁዳ ምድር ሂድ እንጂ በአምባው ውስጥ አትቀመጥ አለው፤ ዳዊትም ተነሥቶ ወደ ሔሬት ዱር መጣ።
6. ሳኦልም ዳዊትና ከእርሱ ጋር የነበሩት እንደ ተገለጡ ሰማ። ሳኦልም በጊብዓ በአጣጥ ዛፍ በታች በኮረብታው ላይ ተቀምጦ በእጁም ጦር ይዞ ነበር፤ ባሪያዎቹም ሁሉ በአጠገቡ ቆመው ነበር።
7. ሳኦልም በአጠገቡ የቆሙትን ባሪያዎቹን። ብንያማውያን ሆይ፥ እንግዲህ ስሙ፤ በውኑ የእሴይ ልጅ እርሻና የወይን ቦታ ለሁላችሁ ይሰጣችኋልን? ሁላችሁንስ ሻለቆችና የመቶ አለቆች ያደርጋችኋልን?
8. ሁላችሁ በላዬ ዶልታችሁ ተነሣችሁብኝ፤ ልጄ ከእሴይ ልጅ ጋር ሲማማል ምንም አይገልጥልኝም፤ ከእናንተም አንድ ለእኔ የሚያዝን የለም፥ ዛሬም እንደ ሆነው ሁሉ ልጄ ባሪያዬን እንዲዶልት ሲያስነሣብኝ ማንም አላስታወቀኝም አላቸው።
9. በሳኦልም ባሪያዎች አጠገብ የቆመው ኤዶማዊው ዶይቅ መልሶ። የእሴይ ልጅ ወደ ኖብ ወደ አኪጦብ ልጅ ወደ አቢሜሌክ ሲመጣ አይቼዋለሁ።
10. እግዚአብሔርንም ጠየቀለት፥ ስንቅንም ሰጠው፥ የፍልስጥኤማዊውንም የጎልያድን ሰይፍ ሰጠው አለ።
11. ንጉሡም የአኪጦብን ልጅ ካህኑን አቢሜሌክን በኖብም ያሉትን ካህናት የአባቱን ቤት ሁሉ ልኮ አስጠራቸው፤ ሁላቸውም ወደ ንጉሡ መጡ።
12. ሳኦልም። የአኪጦብ ልጅ ሆይ፥ እንግዲህ ስማ አለ፤ እርሱም። እነሆኝ፥ ጌታዬ ሆይ ብሎ መለሰ።
13. ሳኦልም። አንተና የእሴይ ልጅ ለምን ዶለታችሁብኝ? እንጀራና ሰይፍ ሰጠኸው፥ ዛሬም እንደ ተደረገው ጠላት ሆኖ ይነሣብኝ ዘንድ እግዚአብሔርን ስለ እርሱ ጠየቅህለት አለው።
14. አቢሜሌክም መልሶ ንጉሡን። ከባሪያዎችህ ሁሉ የታመነ፥ ለንጉሥም አማች የሆነ፥ በትእዛዝህ የሚሄድ፥ በቤትህም የከበረ እንደ ዳዊት ያለ ማን ነው?
15. በውኑ ስለ እርሱ እግዚአብሔርን እጠይቅ ዘንድ ዛሬ ጀመርሁን? ይህ ከእኔ ይራቅ፤ እኔ ባሪያህ ይህን ሁሉ እጅግ ወይም ጥቂት ቢሆን አላውቅምና ንጉሡ እንደዚህ ያለውን ነገር በእኔ በባሪያውና በአባቴ ቤት ሁሉ ላይ አያኑር አለ።
16. ንጉሡም። አቢሜሌክ ሆይ። አንተና የአባትህ ቤት ሁሉ ፈጽማችሁ ትሞታላችሁ አለ።
17. ንጉሡም በዙሪያው የቆሙትን እግረኞች። የእግዚአብሔር ካህናት እጅ ከዳዊት ጋር ነውና፥ ኵብለላውንም ሲያውቁ በጆሮዬ አልገለጡምና ዞራችሁ ግደሉአቸው አላቸው። የንጉሡ ባሪያዎች ግን እጃቸውን በእግዚአብሔር ካህናት ላይ ይዘረጉ ዘንድ እንቢ አሉ።
18. ንጉሡም ዶይቅን። አንተ ዞረህ በካህናቱ ላይ ውደቅባቸው አለው። ኤዶማዊውም ዶይቅ ዞሮ በካህናቱ ላይ ወደቀ፥ በዚያም ቀን የበፍታ ኤፉድ የለበሱትን ሰማንያ አምስት ሰዎች ገደለ።
19. የካህናቱም ከተማ ኖብን በሰይፍ ስለት መታ፤ ወንዶችንና ሴቶችንም፥ ብላቴኖችንና ጡት የሚጠቡትን፥ በሬዎችንና አህዮችንም በጎችንም በሰይፍ ስለት ገደለ።
20. ከአኪጦብም ልጅ ከአቢሜሌክ ልጆች ስሙ አብያታር የሚባል አንዱ ልጅ አምልጦ ወደ ዳዊት ሸሸ።
21. አብያታርም ሳኦል የእግዚአብሔርን ካህናት እንደ ፈጀ ለዳዊት ነገረው።
22. ዳዊት አብያታርን። ኤዶማዊው ዶይቅ በዚያ መኖሩን ባየሁ ጊዜ። ለሳኦል በእርግጥ ይነግራል ብዬ በዚያው ቀን አውቄዋለሁ፤ ለአባትህ ቤት ነፍስ ሁሉ የጥፋታቸው ምክንያት እኔ ነኝ።
23. ነፍሴን የሚፈልግ የአንተን ነፍስ ይፈልጋልና፥ ከእኔም ጋር ተጠብቀህ ትኖራለህና በእኔ ዘንድ ተቀመጥ፥ አትፍራ አለው።

  1Samuel (22/31)