| ← 1Chronicles (14/29) → | 
| 1. | የጢሮስም ንጉሥ ኪራም ቤት ይሠሩለት ዘንድ መልእክተኞችን የዝግባ እንጨትንም ጠራቢዎችንም አናጢዎችንም ወደ ዳዊት ላከ። | 
| 2. | ስለ ሕዝቡም ስለ እስራኤል መንግሥቱ ከፍ ብሎአልና እግዚአብሔር በእስራኤል ላይ ንጉሥ አድርጎ እንዳጸናው ዳዊት አወቀ። | 
| 3. | ዳዊትም በኢየሩሳሌም ሚስቶችን ጨምሮ ሌሎችን ወንዶችንና ሴቶችን ልጆች ወለደ። | 
| 4. | በኢየሩሳሌምም የወለዳቸው የልጆቹ ስም ይህ ነው፤ ሳሙስ፥ | 
| 5. | ሶባብ፥ ናታን፥ ሰሎሞን፥ ኢያቤሐር፥ ኤሊሱዔ፥ | 
| 6. | ኤሊፋላት፥ ኖጋ፥ ናፌቅ፥ ያፍያ፥ | 
| 7. | ኤሊሳማ፥ ኤሊዳሄ፥ ኤሊፋላት። | 
| 8. | ፍልስጥኤማውያንም ዳዊት በእስራኤል ሁሉ ላይ ንጉሥ ሆኖ እንደተቀባ ሰሙ፥ ፍልስጥኤማውያንም ሁሉ ዳዊትን ሊፈልጉ ወጡ፤ ዳዊትም በሰማ ጊዜ ሊጋጠማቸው ወጣ። | 
| 9. | ፍልስጥኤማውያንም መጥተው በራፋይም ሸለቆ አደጋ ጣሉ። | 
| 10. | ዳዊትም። ወደ ፍልስጥኤማውያን ልውጣን? በእጄስ አሳልፈህ ትሰጣቸዋለህን? ብሎ እግዚአብሔርን ጠየቀ። እግዚአብሔርም። በእጅህ አሳልፌ እሰጣቸዋለሁና ውጣ አለው። | 
| 11. | ወደ በአልፐራሲም ወጡ፥ በዚያም ዳዊት መታቸው። ዳዊትም። ውኃ እንዲያፈርስ እግዚአብሔር ጠላቶቼን በእጄ አፈረሳቸው አለ። ስለዚህም የዚያን ስፍራ ስም በአልፐራሲም ብለው ጠሩት። | 
| 12. | አማልክቶቻቸውንም በዚያ ተዉ፤ ዳዊትም አዘዘ፥ በእሳትም አቃጠሏቸው። | 
| 13. | ፍልስጥኤማውያንም ደግሞ በሸለቆው አደጋ ጣሉ። | 
| 14. | ዳዊትም እንደ ገና እግዚአብሔርን ጠየቀ፤ እግዚአብሔርም። ከእነርሱ ዞረህ በሾላው ዛፍ ፊት ለፊት ግጠማቸው እንጂ ወደ እነርሱ አትውጣ። | 
| 15. | በሾላውም ዛፍ እራስ ውስጥ የሽውሽውታ ድምፅ ስትሰማ የፍልስጥኤማውያንን ጭፍራ ሊመታ እግዚአብሔር በፊትህ ይወጣልና በዚያን ጊዜ ወደ ሰልፍ ውጣ አለው። | 
| 16. | ዳዊትም እግዚአብሔር እንዳዘዘው አደረገ፤ ከገባዖንም ጀምሮ እስከ ጌዝር ድረስ የፍልስጥኤማውያንን ጭፍራ መቱት። | 
| 17. | የዳዊትም ዝና በየአገሩ ሁሉ ወጣ፤ መፈራቱንም እግዚአብሔር በአሕዛብ ሁሉ ዘንድ አደረገው። | 
| ← 1Chronicles (14/29) → |